ምስጢረ ሜሮን

ምስጢረ ሜሮን

ምሥጢረ ሜሮን

ሜሮን ቅባት ማለት ሲሆን ለመንፈሳዊ አገልግሎት ብቻ የሚውል የተቀደሰ ቅባት ነው ። የተለያየ መዓዛ ከሚሰጡ ዕፀዋት ተቀምሞና ተነጥሮ ይዘጋጃል ።

በብሉይ ኪዳን ዘመን የነበሩ ካህናት የሚሾሙት ፤ ነገሥታት የሚግሡት ፤ የተቀደሰ ቅብዓ ክህነትናቅብዓ መንግሥት እየተቀቡ ነበር ። ዘፀ 28፥41 ። ዘፀ 29፥7 ፤ ዘሌ 4፥3 ። ዘሌ 6፥20 ። ዘሌ 8፥2 ። 1ሳሙ 9፥16 ። 1ሳሙ 16፥1 ። 1ነገ 1፥34። በዚህ የብሉይ ኪዳን ዘመን ካህናቱም ሆኑ ነገሥታቱ የሚቀቡት ከእስራኤል ዘሥጋ መካከል ተመርጠው የእግዚአብሔርን ህዝብ ለማገልገል ሲሆን ፤ ቅብዓ ክህነቱም ሆነ ቅብዓ መንግስቱ አገልግሎታቸውን በማስተዋልና በታማኝነት እንዲፈጽሙ የሚያተጋቸው የእግዚአብሔር ፀጋ የሚተላለፍበት መንገድ ነው ። በዚህ ዓይነት የመሪነት ቦታ የያዙ ካህናትና ነገሥታት ከእግዚአብሔር የሚሰጣቸውን ትእዛዝ በመቀበል ለእግዚአብሔር እየታዘዙና ህዝባቸውን በቅንነት እያገለገሉ አልፈዋል ።

ቅብዓ ሜሮን በሐዲስ ኪዳን

በብሉይ ኪዳን ለታላቅ መንፈሳዊ አገልግሎት ይውል የነበረው የተቀደሰ ቅብዓት በሐዲስ ኪዳንም መንፈሳዊ ዓላማውን ሳይለቅ አገልግሎቱ ቀጥሏል ። 1 ዮሐ 2፥17። ቅብዓ ሜሮን ከተለያዩ ዕፀዋት ከተቀመመ በኋላ በሊቀ ዻዻስና በዻዻሳት ጸሎትና ቡራኬ ይባረካል።

የቅብዓ ሜሮን አገልግሎት

ሐዋርያት በጸሎተ ሐሙስ ማታ በህጽበተ ዕግር አማካኝነት ተጠምቀዋል ። ዮሐ 13 ፥ 4 ። መንፈስ ቅዱስን የተቀበሉት ግን ጌታችን ባረገ በሀምሳኛው ቀን ነበር ። የሐ ሥ 2፥1 ። በሐዋርያት ዘመን የነበሩ ምዕመናንም አምነው ከተጠመቁ በኋላ እጃቸውን ሲጭኑባቸው መንፈስ ቅዱስ ይወርድላቸው ነበር ። የሐ ሥ 8፥14 ። ጌታችን ሲጠመቅ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል በራሱ ማረፉ ከተጠመቅን በኋላ ሀብተ መንፈስ ቅዱስ እንደሚሰጠን ሲያስረዳን ነው ። ማቴ 3፥16 ። በጥምቀት የተቀበልነው መንፈስ ቅዱስም ካልካድነው በቀር ምንም ኃጢአት ብንሠራ ንስሓ እስክንገባ ይጠብቀናል እንጅ አይለየንም ። ከሐዋርያት በኋላ የተነሱ ሐዋርያውያን አበው (ሊቃነ ዻዻሳት) ከተጠማቂው ህዝብ ብዛት አንጻር ለሁሉ ለማዳረስ እንዲቻልና ለሚቀጥለው ትውልድም የቤተ ክርስቲያን መመሪያ ሆኖ እንዲያገለግል በአንብሮተ ዕድ (እጅ በመጫን) ፋንታ የሚጠመቀው ምዕመን በቅብዓ ሜሮን አማካኝነት ሀብተ መንፈስ ቅዱስ እንዲሰጥ ስለወሰኑ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ቤተ ክርስቲያ ከጥምቀት በኋላ ለተጠማቂው ቅብዓተ ሜሮን በመቀባት መንፈስ ቅዱስን ታድላለች ።
የቃል ኪዳኑ ታቦት (ፅላት) ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ በመንበረ ክብሩ ላይ በመቀመጥ አገልግሎት እንዲሰጥ አስቀድሞ በዚህ በተቀደሰ ቅብዓ ሜሮን ተባርኮ መሰየም አለበት ። ተሰርቆ ወይም በሌላ ፤ ክብሩ በማይጠበቅበትና ተገቢ ባልሆነ ቦታ ቢቆይም ከተመለሰ በኋላ እንደገና መባረክ አለበት ።
ቤተ ክርስቲያን ከታነጸ በኋላ ፤ በውስጡ ሙሉ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ከመስጠቱ በፊት በቅብዓተ ሜሮን መባረክ አለበት ። በቅብዓተ ሜሮን ካልተባረከ ቤተ ክርስቲያን ሊባል አይችልም ። ከተራ አዳራሽ የሚለየው በቅብዓተ ሜሮን ሲከብርና በውስጡም የቃል ኪዳኑ ታቦት ሲኖርበት ብቻ ነውና ።